የአሜሪካ መንግስት የንግድና ጉብኝት(B1/B2) ቪዛ ለማግኘት ብቁ የሆኑ ኢትዮጵያውያን አመልካቶች ቪዛቸውን ከማግኘታቸው በፊት 15,000 የአሜሪካን ዶላር እንዲያሲዙ የሚያስገድድ ህግ አውጥቷል። መንግስት ኢትዮጵያን የቪዛ ዋስትና(Visa Bond) መርሃግብር ውስጥ በማካተቱ ምክንያት ተጓዦች ዋስትና እንዲያሲዙ ይገደዳሉ።
በዋስትና የተያዘው ገንዘብ የሚመለሰው፣ ተጓዦቹ የቪዛ ደንቦችን አክብረው ከተንቀሳቀሱና የቆይታ ጊዜያቸው ሳያልቅ ከአሜሪካ ከተመለሱ መሆኑን በአዲስ አበባ የአሜሪካ ኢምባሲ ስለጉዳዩ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።ይህ መመሪያ ከመጭው መጋቢት 24፣2018 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚሆን የገለጸው ኢምባሲው፣ መመሪያው ከዚህ ቀን በፊት የንግድ ወይም የጉብኝት(B1/B2) ያወጡ ሰዎችን አይመለከትም ብሏል።
ኢምባሲው አመልካቾች ከቃለ መጠይቅ በፊት አስቀድመው ገንዘብ እንዳይከፍሉ አስጠንቅቋል።
“አስቀድሞ መክፈል ቪዛ ለማግኘት ማረጋገጫ አይደለም፤ እንዲሁም ሶስተኛ ወገን ድረ-ገጾች አጭበርባሪዎች ሊሆኑ ይችላሉ።”
ይህ መመሪያ በኤፍ ወይም ኤም(F or M) ቪዛ ወደ አሜሪካ የሚሄዱ ተማሪዎችን እንደመይመለከት ኢምባሲው ገልጿል።













