ሳኡዲ አረቢያ፣ ፓኪስታንና ቱርክ አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ የሚደርስን ማንኛውም ጥቃት ለመመከት የሚያስችል የኔቶ አይነት የጋራ የመከላከያ ስምምነት በዛሬው እለት በሳኡዲ አረቢያ መካ ተፈራርመዋል።
ስምምነቱ ከሶስቱ ሀገራት በአንዳቸው ላይ የሚቃጣ ጥቃት “በሁለም ላይ እንደተቃጣ ይቆጠራል” የሚል ይዘት ያለው መሆኑን ሲኤንኤን ዘግቧል።
ይህ ስምምነት የተደረሰው፣ ሳኡዲ አረቢያ ከበርካታ ግንባሮች ጥቃት በተቃጣባትና ጥቃት ቢፈጸምባት ጣልቃ ለመግባት የሚያስገድድ ሁኔታ ባለበት ወቅት ነው። ሀገራቱ ባወጡት የጋራ መግለጫ እንደገለጹት ስምምነቱ ጥቃትን በጋራ ለመከላከልና በመካከላቸው ያለውን ሁሉንአቀፍ የመከላከያ ትብብር ለማሻሻል ያለመም ነው።
ስምምነቱ በእስልምና ሃይማኖት ዘንድ ቅዱስ በሆነችው መካ መፈረሙ፣ ሃይማኖታዊና ፖለቲካ እንድምታ ይኖረዋል ተብሏል።
ሳኡዲ አረቢያ በአለም ቀዳሚ ከሆኑት የነዳጅ ላኪዎች አንዷ ስትሆን ፓኪስታን ደግሞ ኑክሌር የታጠቀች ብቸኛዋ የሙስሊም ሀገር ነች። ስምምነቱ የተደረሰው የቱርኩ ፕሬዝዳንት ታይፕ ኤርዶኻን፣ የሳኡዲው ልኡል አልጋወራሽ ሞሀመድ ቢን ሳልማን እና የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሻባዝ ሻሪፍ ውይይት ማድረጋቸውን ተከትሎ ነው።









