በፈረንሳይ የተከሰተው ከባድ የሙቀት ሞገድ የሀገሪቱን ሆስፒታሎችና የድንገተኛ ጊዜ አገልግሎቶችን እያጨናነቀ ባለበት ወቅት፣ የሀገሪቱ ባለስልጣናት በፓሪስ ያሉ መጠጥ ቤቶች አልኮል እንዳይሸጡ ከልከላ ጥለዋል።
ሮይተርስ የፓሪስን ፖሊስ ጠቅሶ እንደዘገበው በህዝብ ቦታዎች(public palces) አልኮል መጠጣት ከትናንት ከሰአት ጀምሮ ተከልክሏል። ከዚህ በተጨማሪ ሰዎች ቅዳሜ እና እሁድ ከ12 ሰአት እስከ አንድ ሰአት ድረስ አልኮል ይዘው ወደ ቤታቸው እንዳይሄዱ ተደርጓል።
ይህ ውሳኔ የተላለፈው የሰውነት ድርቀትንና የራስ ህመምን አደጋን ለመቀነስ መሆኑን የገለጹት ባለስጣናቱ አልኮል ከፍተኛ ሙቀትን ተከትለው የሚመጡ ችግሮችን እንደሚያባብስ አስጠንቅቀዋል። ባለስለጣናት እንደሚሉት ከሆነ እርምጃው ከሙቀት ጋር በተያያዙ ችግሮች የተጨናነቁትን ሆስፒታሎችና የድንገተኛ ህክምና አገልግሎቶች ጫናን ለመቀነስ ያለመ ነው።
የፈረንሳይ ኦርሳን የድንገተኛ ጤና እቅድ ወደ ተግባር ገብቷል። ይህ እቅድ ሆስፒታሎች የሰራተኞቻቸው ቁጥር እንዲጨምሩ፣ በጤና ስርአቱ ውስጥ ትብብር እንዲጠናከር እንዲሁም እንደአስፈላጊነቱ አስቸኳይ ያልሆኑ ህክምናዎች ቀጥሮ እንዲራዘም ይፈቅዳል።
በፓሪስ እና በዙሪያዋ ያሉ ሆስፒታሎች አሁን ላይ በታማሚዎች “የተጨናነቁ” ሲሆን የእሳት አደጋ ሰራተኞች ደግሞ ሙቀቱን ተከትሎ እሳት ሊነሳ ይችላል በሚል ስጋት ጫና ውስጥ ገብተዋል።
ባለስልጣናት ከፍተኛው የሙቀት መጠን እየቀጠለ በመሆኑ በተለይ በእድሜ የገፉ ሰዎች፣ ህጻናትና ተያያዥ ህመም ያለባቸው ሰዎች ከጸኃይ እንዲርቁና ቀዝቃዛ ቦታዎችን እንዲያዘወትሩ አሳስበዋል።











