በአፍሮ-ኢንሳይት
ጳጉሜ 2018
ጠንካራ የብሪክስ ትብብር ኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት እንድትስብ፣ የወጪ ንግዷን እንድታስፋፋና የኢንዱስትሪ ልማት ግቧን እንድታሳካ ሊረዳት እንደሚችል የኢኮኖሚ ባለሙያው ፍፁም ግርማ ተናገሩ።
18ኛው የብሪክስ ጉባኤ መስከረም 2 እና 3፣ 2019 በኒው ዴልሂ የአባልና የአጋር አገራት መሪዎችን ያሰባስባል። ንግድ፣ የልማት ፋይናንስና የዓለም አቀፍ ሥርዓቱ ማሻሻያ በጉባኤው ዋና ዋና መወያያዎች እንደሚሆኑ ይጠበቃል።
ለኢትዮጵያና ለሌሎች የአፍሪካ አባል አገራት፣ ጉባኤው የኢንዱስትሪ ልማትን የሚደግፍ፣ የፋይናንስ ተደራሽነትን የሚያሻሽልና የአፍሪካ ምርቶች በዓለም ገበያዎች ጠንካራ ቦታ እንዲይዙ የሚያስችል ተግባራዊ ትብብር ለመጠየቅ ዕድል ይሰጣል።
የኢኮኖሚ ባለሙያው ፍፁም ግርማ ለአፍሮ-ኢንሳይት በሰጡት ልዩ ቃለ ምልልስ፣ የብሪክስ መሪዎች ይበልጥ ፍትሐዊና ሁሉን አካታች የዓለም አቀፍ ሥርዓት ለመገንባት ያላቸውን ቁርጠኝነት እንደገና እንደሚያረጋግጡ እንደሚጠብቁ ተናግረዋል።

“መጪው ጉባኤ ብሪክስ ይበልጥ ፍትሐዊና እኩልነት የሰፈነበት ዓለም አቀፍ ሥርዓት ለመገንባት ያለውን የማይናወጥ ቁርጠኝነት የሚያረጋግጥበት መድረክ እንደሚሆን እጠብቃለሁ፣” ሲሉ ፍፁም ተናግረዋል።
እንደ ፍፁም ገለጻ፣ ብሪክስ ታዳጊ ኢኮኖሚዎች ቅድሚያ የሚሰጧቸውን ጉዳዮች እንዲያቀርቡ ሰፊ ቦታ ስለሚሰጥ ለታዳጊ አገራት ያለው ጠቀሜታ እያደገ መጥቷል።
“የብሪክስ ትብብር በኢኮኖሚና በፖለቲካ ዘርፎች የሚገኙ ዕድሎችን እያሰፋ መጥቷል፣” ያሉት ፍፁም፣ ሁለገብ ትብብሩና የፖሊሲ ውይይቶቹ ለታዳጊ አገራት ይበልጥ ጠንካራ ውክልና እንደሚሰጡ ጠቁመዋል።
ቻይና ለብሪክስ ከፍተኛ የኢኮኖሚ አቅም ታክላለች
ቻይና ባላት ግዙፍ ኢኮኖሚ፣ በመሥራች አባልነቷና በዓለም ደቡብ አገራት ውስጥ ባላት ሰፊ ግንኙነት ምክንያት በጉባኤው ማዕከላዊ ሚና እንደምትጫወት ይጠበቃል።
“ቻይና ብሪክስ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ቀዳሚ ሚና ስትጫወት ቆይታለች፤ የብሪክስን ትብብር በማጠናከርም ሊተካ የማይችል ሚና ነበራት፣” ሲሉ ፍሱም ገልጸዋል።
ቻይና በንግድ፣ በመሠረተ ልማት ኢንቨስትመንትና በሻንጋይ የሚገኘውን አዲስ የልማት ባንክ በመሳሰሉ ተቋማት ባላት ተሳትፎ ለብሪክስ ተጨባጭ የኢኮኖሚ አቅም እንዲኖረው አግዛለች።
ፍፁም የቤልት ኤንድ ሮድ ኢኒሼቲቭንና ቻይና የዓለም የፋይናንስ ሥርዓት እንዲሻሻል የምታደርገውን ድጋፍም ጠቅሰዋል።
“ቻይና በድጋሚ ቁልፍ ተሳታፊ በመሆን ለብዙዎች ጠቃሚ የሆኑ ተጨማሪ ኢኒሼቲቮችና ቁርጠኝነቶችን ይዛ እንደምትቀርብ እጠብቃለሁ፣” ብለዋል።
በ2025 የቻይናና የአፍሪካ ንግድ 348 ቢሊዮን ዶላር በመድረሱ የቻይና ጠቀሜታ በአኅጉሪቱ ያላትን ተጽዕኖ ያሳያል።
ከግንቦት 1፣ 2026 ጀምሮ ቻይና የዲፕሎማሲ ግንኙነት ካላት 53 የአፍሪካ አገራት ለሚገቡ ምርቶች ከቀረጥ ነፃ የሆነ የገበያ መዳረሻ ሰጥታለች። ይህም ብዙ የአፍሪካ ምርቶች ወደ ቻይና ገበያ እንዲገቡ ሊያግዝ ይችላል።
ሆኖም የቀረጥ ቅነሳ ብቻውን በቂ አይሆንም። የአፍሪካ አምራቾች በቂ ምርት ማቅረብ፣ የቻይናን የገቢ ምርቶች መስፈርት ማሟላትና ምርቶቻቸውን በተወዳዳሪ ወጪ ማጓጓዝ ይኖርባቸዋል።

ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቅድሚያዎቿን ማራመድ ትችላለች
ኢትዮጵያ “እአ በ2024 መጀመሪያ የብሪክስ አባል ሆናለች። አቶ ፍፁም አባልነቱ አገሪቱ የልማት ቅድሚያዎቿን የምታራምድበት ጠንካራ ዓለም አቀፍ መድረክ እንደሚሰጣት ገልጸዋል።
“ብሪክስ ከኢትዮጵያ ቅድሚያዎች ጋር የሚጣጣሙ ሰፊ ዕድሎችን ይዞ መጥቷል፣” ብለዋል።
ንግድ፣ ኢንቨስትመንትና የኢንዱስትሪ ፋይናንስ ኢትዮጵያ ተጠቃሚ ልትሆንባቸው የምትችላቸው ዋና ዘርፎች እንደሆኑ ፍሱም ጠቁመዋል።
በብሪክስ አባላት መካከል ያለው ጠንካራ ትብብር ለኢትዮጵያ ምርቶች ተጨማሪ ገበያዎችን ሊከፍትና አገሪቱ ከቻይናና ከሌሎች አባላት ኢንቨስትመንት እንድትስብ ሊያግዝ ይችላል።
ኢትዮጵያ ከብሪክስ ጋር ከተያያዙ ተቋማት የሚገኝ ፋይናንስ ተጠቃሚ ልትሆን ትችላለች። አዲሱ የልማት ባንክ ኢትዮጵያን ተቀብሏታል፤ ሆኖም አገሪቱ የአባልነት ሂደቷን እስክታጠናቅቅ ድረስ የወደፊት አባል ተብላ ተዘርዝራለች።
ሂደቱን ማጠናቀቅ ኢትዮጵያ ለመሠረተ ልማትና ለዘላቂ ልማት ፋይናንስ ለመጠየቅ የተሻለ ቦታ እንዲኖራት ሊያደርግ ይችላል።
የብሪክስ አባልነት በራሱ ኢንቨስትመንትን ወይም በተመጣጣኝ ወጪ ፋይናንስን አያረጋግጥም። ኢትዮጵያ ተአማኒ ፕሮጀክቶችን፣ ውጤታማ ተቋማትንና የአገር ውስጥ ንግዶች አዳዲስ የገበያ ዕድሎችን እንዲጠቀሙ የሚያስችል የወጪ ንግድ ስትራቴጂ ያስፈልጋታል።
አፍሪካን ከዓለም አቀፍ የአቅርቦት ሰንሰለቶች ማገናኘት
የብሪክስ ትብብር የትራንስፖርት፣ የኃይል፣ የሎጂስቲክስና የዲጂታል መሠረተ ልማቶችን በመደገፍ የአፍሪካን ኢኮኖሚያዊ ውህደት ሊያጠናክር እንደሚችል ፍፁም ያምናሉ።
እንዲህ ያለው ኢንቨስትመንት በአፍሪካ ገበያዎች መካከል ምርቶችን የማጓጓዝ ወጪ በመቀነስ የአፍሪካ አኅጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣናን ሊደግፍ ይችላል።
አቶ ፍፁም ቻይና ልትጫወታቸው የምትችላቸውን ሁለት ዋና ዋና ሚናዎች ጠቁመዋል። የመጀመሪያው ከአፍሪካ ተጨማሪ ምርቶችን በመግዛት የአፍሪካ አምራቾችን ከዓለም አቀፍ የአቅርቦት መረቦች ጋር ማገናኘት ነው።
“ቻይና በዓለም አቀፍ የግዥ ስትራቴጂዋ ውስጥ የአፍሪካን የማምረት አቅምና ሀብቶች በይበልጥ በመጠቀም የድርሻዋን ልትወጣ ትችላለች፣” ብለዋል።
ሁለተኛው ሚና የቴክኖሎጂ ሽግግርን፣ የቴክኒክ ሥልጠናንና የክህሎት ማዳበሪያ መርሐ ግብሮችን ማስፋፋት ነው። ይህ ትብብር የአፍሪካ ኢኮኖሚዎች በጥሬ ዕቃዎች የወጪ ንግድ ላይ ጥገኛ ከመሆን ወጥተው ተጨማሪ የተመረቱና ከፍተኛ እሴት ያላቸውን ምርቶች እንዲያቀርቡ ሊረዳቸው ይችላል።
በኒው ዴልሂ የሚካሄደው ጉባኤ ለኢትዮጵያና ለሌሎች የአፍሪካ አባላት የብሪክስን የወደፊት አቅጣጫ ለመቅረጽ ዕድል ይሰጣል።
የጉባኤው ጠቀሜታ የሚለካው ፋይናንስ ባገኙ ፕሮጀክቶች፣ በተቀነሱ የንግድ ወጪዎች፣ በተላለፉ ክህሎቶችና በተስፋፋ የወጪ ንግድ ይሆናል።
ቻይና ይህንን አጀንዳ ለማራመድ የሚያስችል የኢኮኖሚ አቅምና ሰፊ ገበያ አላት። በመሆኑም የቻይና ተሳትፎ የብሪክስን ቃል ኪዳኖች ለኢትዮጵያና ለመላው የአፍሪካ አኅጉር ተጨባጭ ጥቅሞች ለመለወጥ ወሳኝ ይሆናል።












