የኔፓልና የቻይና የነፍስ አድን ሰራተኞች፣ በሂማልያ ተራራ ላይ ያለውን የበረዶ ክምር መንሸራተት ተከትሎ በተፈጠረው ከባድና የጎርፍ አደጋ ምክንያት የጠፉ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ለማግኘት እየተጣደፉ ናቸው።
ባለስለጣናት እስከዛሬ ጠዋት ድረስ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 750 መድረሱንና ሌሎች ከ3000 በላይ ሰዎች ደግሞ የደረሱበት አለመታወቁን ገልጸዋል። ባለፈው ረቡዕ በኔፓልና በቻይና ድንበር ላይ የተከሰተው ይህ ከባድ የጎርፍ አደጋ በሸለቆች ዳርቻ ላይ የተሰሩ መኖሪያ መንደሮችን በመጠራረግ ከፍተኛ ውድመት አስከትሏል።
የአለም ቀይ መስቀል ማህበር እንደገለጸው በአደጋው ከ90,0000 በላይ የሚሆኑ ነዋሪዎች ህይወት ተመሰቃቅሏል።ይህ በቅርብ አመታት ውስጥ የተከሰተ ድንበር ዘለል አደጋ እንደሆነና የነፍስ አድን ስራውም ከባድ ፈተና እንደገጠመው የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከኔፓል አቻቸው ጋር በስልክ ባደረጉት ውይይት ተናግረዋል።
የኔፓል የአደጋ ጊዜ ባለስልጣን 734 ሰዎች ሲሞቱ ሌሎች 2498 ሰዎች ደግሞ የደረሱበት አልታወቀም ብሏል። በነፍስ አድን ስራው 7514 ሰዎችን ህይወት ማትረፉ መቻሉን ባለስጣኑ አክሏል። በቻይና በኩል ደግሞ 16 ሰዎች ሲሞቱ ሌሎች 546 ሰዎች ደግሞ ጠፍተዋል።
በዚህ አደጋ ከ23 ሀገራት የመጡ 261 ሰዎች ቲቤት ውስጥ ወደ ኔፓል ለማቋረጥ መሳኝ በሆነው ቦታ የደረሱበት ጠፍቷል። አደጋው መጠነሰፊ በመሆኑ በተራራማው የሂማሊያ አካባቢ ያለውን የነፍስ አድን ስራ አወሳስቦታል።
የኔፓል ባለስልጣናት በአደጋው የሞቱ ሰዎችን አስከሬን በጅምላ በመቅበር ላይ ናቸው።












